የከተማዋ መዋቅራዊ ፕላን በተግባር ከሚተገበርባቸው ዋና ዋና ዘርፎች አንዱ የመንገድ ዘርፍ ነው። በዚህ ረገድ የአዲስ አበባን የመንገድ መሰረተ ልማት የመገንባት፣ የመንከባከብ እና የመምራት ኃላፊነት የተሰጠው የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለስልጣን፤ የመንገድ መሰረተ ልማት ሥራዎችን በሁሉም የከተማዋ ማዕዘናት ተደራሽ ለማድረግ እየሰራ ይገኛል።
ባለሥልጣን መስሪያ ቤቱ በየጊዜው በከተማዋ የሚሻሻሉ መዋቅራዊ እቅዶችን መሰረት በማድረግ እና የትራፊክ ሁኔታዎችን እንዲሁም የልማት ጥያቄዎችን በማጤን ይሰራል፡፡. በተለይም ባለፉት ሰባት ዓመታት የከተማዋን የመንገድ ሽፋንና ተደራሽነት ለማስፋት በመደበኛ የመንገድ ግንባታና የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች ከፍተኛ ጥረት ተደርጓል።
ዘመናዊ የተሽከርካሪ ማመላለሻ ኮሪደሮች፣ ሰፊና ምቹ የእግረኛና የብስክሌት መንገዶች፣ ትላልቅ የትራፊክ ማሳለጫ ድልድዮች እና ከመሬት በታች የተሽከርካሪ መተላለፊያ መንገዶች ተሰርተው የከተማዋን የመንገድ ዘርፍ ወደ አዲስ የእድገት ምዕራፍ ለማሸጋገር አስችሏል። ነባር መንገዶችን በማሳደግና አዳዲስ መንገዶችን በመገንባት የተመዘገቡት ድሎች በመዲናችን የትራፊክ እንቅስቃሴን ምቹና ቀልጣፋ ከማድረግ ባለፈ የከተማዋን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ልማት ለማፋጠን ከፍተኛ አስተዋፅኦ አበርክተዋል።
በሌላ በኩል በአሁኑ ወቅት በከተማዋ ያለው የመንገድ አውታር ደህንነቱ የተጠበቀ ሆኖ ተገቢውን አገልግሎት እየሰጠ እንዲቀጥል መደበኛ እና ወቅታዊ የመንገድ ጥገና ስራዎች እየተሰሩ ነው። በተጨማሪም የትራፊክ ፍሰቱን የተስተካከለ ለማድረግ የመልሶ ማልማት ስራዎች በስፋት እየተሰሩ ይገኛሉ።
በመንገድ ዘርፍ የሚሰጠውን አገልግሎት የበለጠ ለማሻሻል ባለሥልጣን መስሪያ ቤታችን በቅርቡ ሁሉን አቀፍ ተቋማዊ ማሻሻያ አድርጓል። ይህ ማሻሻያ ተቋሙ በቀጣይ የላቀ አፈጻጸም እንዲያስመዘግብና የተቀላጠፈ የሀብት አጠቃቀምን በማስተዋወቅ ተልዕኮውን በብቃት እንዲወጣ ያስችለዋል።
በመጨረሻም ይህ እድገት የሚያስመሰግነው ቢሆንም የከተማችን ነዋሪዎች በከፍተኛ የመንግስትና የህዝብ ሃብት የተገነቡ የመንገድ መሰረተ ልማቶችን እንዲጠብቁ፣ እንዲንከባከቡ እና በአግባቡ እንዲጠቀሙበት በዚህ አጋጣሚ ለማስታወስ እወዳለው፤
የተሻለ መንገድ ለተሻለች አዲስ አበባ!
አመሰግናለሁ።