በግንባታ እንቅስቃሴዎች ሳቢያ በመንገድ ሀብት ላይ እየደረሰ ያለው ጉዳት አሳሳቢ ሆኗል
አዲስ አበባ፣ መስከረም 16 ቀን 2016 ዓ.ም፡- አዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለስልጣን የከተማዋን የመንገድ ሽፋን ለማሳደግና የትራፊክ ፍሰቱን ይበልጥ ምቹ ለማድረግ በየዓመቱ በከፍተኛ በጀት የመንገድ ግንባታና ጥገና ሥራዎችን በማከናወን የከተማችንን ነዋሪዎች ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሠራ ይገኛል።
ይሁን እንጂ በመንገድ ሀብት አጠቃቀም ጉድለትና ኃላፊነት በጎደለው ህገ-ወጥ ተግባራት ሳቢያ በመንገድ ሀብት ላይ በየጊዜው እየደረሰ ያለው ጉዳት አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሷል።
ለአብነትም በጀሞ አካባቢ እየተከናወነ በሚገኘው የጤና ተቋም ግንባታ ምክንያት፣ በአካባቢው የሚገኘው የወንዝ ውሃ መውረጃ መስመር በመዝጋቱና ወደ መንገድ እየፈሰሰ ባለው ውሃ የአካባቢው የአስፋልት እና የኮብል መንገድ ለጉዳት ከመጋለጡም ባሻገር የትራፊክ እንቅስቃሴው እየተስተጓጎለ ይገኛል፡፡
የደቡብ አዲስ አበባ መንገድ ሀብት አስተዳደር ቡድን መሪ ኢንጂነር ኃይሉ ደመቀ እንደገለፁት ችግሩን ለመፍታትና የማስተካከያ እርምጃ እንዲወሰድ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የግንባታ ፈቃድና ቁጥጥር ባለስልጣን በማሳወቀ ክትትል እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የከተማዋ የመንገድ አውታሮች ለረጅም ጊዜያት ተገቢውን አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ፣ በልዩ ልዩ የግንባታ ሥራዎች ላይ እየተሳተፉ የሚገኙ አካላት በመንገድ ሀብት ላይ ጉዳት ከሚያደረሱ ህገ-ወጥ ድርጊቶች በመቆጠብ የበኩላቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ያሳስባል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ማህበራዊ ትስስር ገፆችን ይቀላቀሉ:-
ቴሌግራም:- https://t.me/AddisRoads
ፌስ ቡክ :- https://www.facebook.com/AbabaCity
ትዊተር :- https://twitter.com/AbabaCity
ኢንስታግራም፡- https://www.instagram.com/addisababaroads/
